ዲሂዩማናይዜሽን (ሰብአዊ ፍጡርነትን መንሳት) የዘር ፍጅት እሳት ማራገቢያ ኻልኣዩ ኣብርሃ 12-16-21 ማስገንዘቢያ ይህ ፅሁፍ የፓለቲካ ክርክርን ከፍ ባለ ደረጃ ለሟጧጧፍ የታለመ ሳይሆን ህዝብ የስልጣን ፍላጎት ባሰከራቸው የፓለቲካ መሪዎች እየተገፋ በወገኑ ላይ፣ በአገሩ ልጅ ላይ፣ በጎረቤቱ ላይ በጭፍንነት ለትውልድና ለታሪክ የሚተርፍ ግፍ እንዳይሰራ ለማስገንዘብ እንዲረዳ አለም መዝግቦ ካኖራቸው ዘግናኝ ታሪኮች በጭልፋ የቀዳሁትን ለማካፈል ያለምኩበት ነው። የግፍ ታሪክ መተረክ ለተራኪው ጤና ይነሳል። ነገር ግን አሁንም ተመሳሳይ ሁኔታዎች እየተከሰቱ ስለሆነ የልብ ትርታን የሚጨምር ቢሆንም ህዝቦችንን ለማስጠንቀቅ ሲባል ስለ እብደቶች መፃፍና መናገር የግድ ይላል። ፅሁፉ ባለፈው ሳምንት የኸርማን ጌሪንግን ጥቅስ እንደርእስ ተሰጥቶት በዓይጋ ፎረም ላይ ላወጣሁት ሃተታ ተከታይ ሊሆን ይችላል።
1. ረዥም መንደርደሪያ በተለያዩ የአለም ክፍሎች ሰዎች በሌሎች ሰዎች ላይ ተነስተው የፈፀሟቸው ዘግናኝ ድርጊቶች “የሃይማኖት አምባ”፣ የግዜር “የስለት ልጅ” እየተባለች በምትንቆለጳጰሰው በኢትዮጵያ ውስጥ ሲታቀዱም ሲተገበሩም ይታያል። የትግራይ ህዝብ በማህበራዊ እድገት ደረጃው፣ በረዥም ታሪክ ባለቤትነቱ፣ ሰብአዊአዊነት የተላበሰ ጀግንነቱ ከፍ ካለ ማማ ላይ የተቀመጠ ህዝብ ነው። የማህበራዊ እድገት ደረጃችን ከሌላው ከፍ ያለ ነው ብለው ከሚታበዩትና ከነሱ ዝቅ ያለ ነው ብለው በመደቡት ላይ እብሪት ከሚፈፅሙት ጋር የማይመሳሰል ዘውድ የሆነ ባህርይ ባለቤት የሆነ ህዝብ ነው። የትግራይ ህዝብ ከልሂቅ እስከ ደቂቅ በበላይነት ስሜት ተነሳስቶ ሌላውን ለመድፈቅና የእድሜ ልክ ባርያ አድርጎ የመግዛት ባህል የለውም። ይልቁንስ ለተጨቆኑ ፍትህ ለማስገኘት የሚተጋ የተመረጠ ህዝብ ነው። ይህ ጉራ አይደለም። ከነሱ የተለየውን የሰው ፍጥረት የማይመስላቸው፣ ተዋግቶ የሚያሸንፍ፣ ነግዶ የሚያተርፍ፣ ነግሶ የሚመራ፣ ሰርቶ የሚያመርት፣ ተናግሮ የሚያሳምን፣ ተምሮ የሚበቃ፣ ፀልዮ የሚሰማ ያለ የማይመስላቸው ሁሉ አይናገሩት እንጂ የትግራይ የሞራል ከፍታን ውስጣቸው አሳምሮ ያውቀዋል። ይህንን ህዝብ ነው ከ80 ብሄር ብሄረሰብ ነጥለው በቃላት ውርጅብኝ አነሳስተው በተገኘው ዘዴ ከምድረ ገፅ ለማጥፋት ቆርጠው የተነሱት። በትግራይ ህዝብ ላይ ይህን ለመፈፀም ያነሳሳቸው ምክንያት አንድ ቢሆንም እውነተኛውን ምክንያት በመደበቅ ህዝብን የሚያሳብዱበት ግን ሌላ ዘዴ አላቸው። ከሆዳቸው ውስጥ ያለው ዋናው ምክንያት የኢምፔርያል አሃዳዊ አገዛዝ አንደኛ ጠላትና የጠቅላይ አገዛዝ ህልማቸው ዋና እንቅፋት አድርገው የወሰዱት ከሰማንያ ብሄር ብሄረሰብ አንዱ የሆነው የትግራይን ህዝብ ነው። ህዝብን በአጠቃላይ መወንጀልና በህዝብ ላይ ማነሳሳት ብዙም ተቀባይነት ስለማይኖረው በትግራይ ህዝብ ላይ የማነሳሳቱ ተግባር ትኩር ብሎ ላላስተዋለው መስሎ የሚታየው “ጥቂት” በሚባሉ መሪዎች ላይ የሚካሄድ ዘመቻ እንደሆነ ነው። “ህወሓት ካልጠፋች ኢትዮጵያ መቸውም ሰላም አታገኝም” ይሉታል ጭንቀታም መሆኑን አሳምረው ለሚያውቁት የኢትዮጵያ ህዝብ። ህወሓትን እያደንን ነው እያሉ ግን የትግራይን ህዝብ ይፈጁታል፣ ይዘርፉታል፣ ያወድሙታል። ይህን ባደረጉ መጠን የህወሓትና የህዝቡ ጥምረት እየጠነከረ ይሄዳል። ጥምረቱ ለህወሓት አይበገሬነት ምክንያት ሲሆን በንዴትና ተስፋ መቁረጥ ይሉኝታቸውን ጥለው በቀጥታ በህዝቡ ላይ ዘምተዋል። ራሳቸው ቁጣና ምሬትን በህዝብ ዘንድ አሳድረው የትግራይን ህዝብ በያለበት “ሽብርተኛ ድርጅት ደገፍክ” እያሉ ይወነጅሉታል። “ሽብርተኛ” ሲባል የኢትዮጵያ ህዝብ ቶሎ በአእምሮው የሚመጣው ፎቆችን አውድሞ ኒውዮርክ ላይ 3000 ንፁሃንን ያጠፋው ቢላደን፣ ኢትዮጵያውያንን አሰልፈው አንገታቸውን የቀሉት አይሲሶች ናቸው። እነዚህ የኢትዮጵያ መሪዎች በህዝቡ ላይ የስነ አእምሮ ጌም እየተጫወቱ ነው። መቐለ ያሉት ምርኮኞች የሚሉትም ይህንን ነው:-“እንዳትማረኩ፣ ከያዟችሁ ያርዷችኋል ተብለናል”። ትክክለኛ ሽብርተኞች ለራሳቸው ስልጣን መጠበቅ ሲሉ ወደ አላስፈላጊ መስዋእትነት የላኳቸው እንጂ በሰብአዊነት የተቀበሏቸው እውነተኛ ጀግኖቹ አለመሆናቸውን ተገነዘቡ። ከጅብ መሃል ሳይሆን ከሃይማኖተኛ ህዝብ እጅ መግባታቸውን ሲያዩ ልደታቸውን እያከበሩና የመቐለ ልጆች ወልደው እየሳሙ ነው። የትግራይ ህዝብ የሚወደድበት ብቻ ሳይሆን የሚመለክበት ጊዜ ሩቅ አይደለም። ፃድቅ ከጭፍጨፋ በኋላ ነው ቤተ ክርስትያን የሚሰራለት፣ ህዝቡ ያጠፋውን አጥፍቶ ከእብደት ከወጣ በኋላ። አሁንማ ጀሮው ጥይትን እንጂ ቃላትን አይሰማም። ለዚህም ነው የትግራይ ወጣት ትውልድ ትምህርቱን፣ ወላጆቹን፣ ስራውን ትቶ በየግንባሩ የሚዋደቀው። አቢይ ትግራይ ሄዶ የተለገሰው ጭብጨባ መልእክቱ ምን ነበር? “ጥሩ አስተዳዳሪ ከሆንክ ለኛ የግድ ትግሬ መሆን የለብህም” የሚል ነበር። ታድያ አቢይ “ሞተር” ያለውን “ጅብ ነህ” ብሎ ሊያጠፋው ቢመጣ ከአመራሩ ጋር አንድ ሆኖ ራሱን ላይከላከል ነው? “አንቺው ታመጪው አንቺው ታሮጪው”! አመራርን ለማጥፋት የኢትዮጵያን ህዝብ ማነሳሳት ላያስፈልግ ይችላል። በቲዮሪ በጥቂት ቀናት ውስጥ አምሳ የማይሞሉ የህወሓት አመራሮችን ማጥፋት ቀላል ነው። ምንም እንኳን አምሳዎቹን አመራሮች የፈጠራቸው ህዝብ በመሆኑ አሁንም ሌላ አምሳ ሊተካ እንደሚችል ቢታሰብም “የፊት የፊቱን” እንዳለው ጓያ ነቃይ ህገ መንግስቱን ቀይረው ጠቅላይ ግዛቶችን እስኪያደራጁ ድረስ ፋታ ይሰጣቸዋል። ምንጩን ማድረቅ የሚመኙ ቢሆንም የተገኘውን ይጠቀማሉ። ይህ ግን ሊሆን አልቻለም፣ አመራሮቹን ለማጥፋት አልተቻለም። ይህ የሆነው ትግራይ ውስጥ ህዝቡና አመራሩ ዉሃና ወተት ሆነው በመቀላቀላቸው ነው። ህዝብና አመራር የሚቀላቀሉት አንዱ የሌላኛው የህልውና ዋስትና ሆኖ ሲገኝ ነው። ህዝብና አመራር በተፈጥሮ ዉሃና ዘይት የመሆን ባህርይ አላቸው። ዘይቱን ከውሃው ለመለየት ቀላል ባይሆንም የማይቻል ግን አይደለም። አመራርና ህዝብ ዘይትና ውሃ ሳይሆን ወተትና ዉሃ እንዲሆኑ የሚያደርጋቸው በሁለቱም ላይ የተነሳ ጠላት ሲኖር ነው። ዉሃና ወተትን ለይቶ ወተቱን መድፋት ስለማይቻል ያለው አማራጭ አንድ ላይ መድፋት ነው። “አሳን ለመያዝ ውሃውን ማድረቅ ነው” ከተባለ ሁለቱንም አንድ ላይ ማጥፋት መሆኑ ነው። ህዝብን ጨርሰህ ለማጥፋት ከተፈለገ ደግሞ በጦር ሃይል ብቻ የሚቻል አይደለም። ይህን አቢይ ባህር ዳር ላይ በይፋ ተናግሮታል:- “በጦር አልተቻለም፣ ህዝብን ማነሳሳት አለብን”!! “ዋናው ኮማንደር” ኢሳት እኮ ቀደም ብሎ ምክር ለግሷል:- “95 ሚልዮን የኢትዮጵያ ህዝብ በ 5 ሚልዮን የትግራይ ህዝብ ላይ ተነስ”።
ሚልዮኖችን በሚልዮኖች ላይ ማነሳሳት ቀላል ነገር አይደለም። እንዲሁ “የኢትዮጵያ ህዝብ ሆይ! ሆ ብለህ ተነስና የትግራይን ህዝብ አጥፋ” በማለት ብቻ የሚሞከር አይደለም። ይህን የሚሞክር ሰው በቅርቡ ከአማኑኤል ሆስፒታል “ኤፎችን” ተከናንቦ በክሪስማስ የተመረቀ ደደብ እብድ ነው መባሉ አይቀርም (ሳቅ በሳቅ)። ህዝብን በህዝብ ላይ ማነሳሳትና ጥፋት ማድረስ የሚሳካው የሚያነሳሳው ሳይሆን የሚነሳሳው ራሱ እብድና ጨካኝ እንዲሆን ሲደረግ ነው። ለስልጣናቸው ቀናኢ የሆኑ መሪዎች በተቀናቃኛቸው ላይ ለማነሳሳት ህዝብን እብድና ጨካኝ እንዲሆን የሚያደርጉት በምን ምትሃት ነው? የሚል ጥያቄ ወሳኝ ጥያቄ ነው። ይህንን ጥያቄ ነው በዚህ ፅሁፍ ለመመለስ የምሞከረው። በታዳጊ አገሮች በየደረጃው ያለው ከጠቅላይ ሚኒስትር እስከ የሱቅ ጥበቃ ሃላፊ ድረስ ያለው ስልጣን ተጨማሪ ገንዘብ የሚገኝበት እድል ብቻ ሳይሆን የህልውናም ጉዳይ ጭምር ነው። በባለፀጋ አገሮች የግል ፋብሪካ እያለው መሪ የሆነ ሰው ጥፋት የሰራ ከመሰለው በራሱ ከስልጣን ይለቃል። ፊትም ቢሆን የሚበላው አጥቶ ሳይሆን ለዝና ይሆናል ስልጣን የሚይዘው። ልጆቹን የሚያስተምርበት ገንዘብ ያልነበረው ሚኒስትር ሲሆን መኪናና አበል ጥሎ መውረድ ሞት ነውና አጥፍቶ መጥፋትን ይመርጣል። “ደግነቱ” እሱና ልጆቹ ሳይሆኑ አጥፍቶ የሚጠፋለት ተራው ህዝብ ነው። መሪዎች ስልጣናቸውን ለመጠበቅ ሲሉ ህዝብን እንዴት እንደሚያነሳሱትና ለምን ሰብሉን ማሳ ላይ ለወፍና ለዝንጀሮ ሰጥቶ፣ የሚሳሳላቸው ሚስትና ልጆቹን ከቤት ትቶ፣ ቆመህ ጠብቀኝ ይሁን የሽንኩርት መክተፊያ ይዞ ፀላእተ ሰናይ እንደወረሰው ታማሚ ሆኖ እያቅራራ ወደ ሞቱ እንዲያመራ አድርገው ናላውን እንደሚያዞሩት እናያለን። አነሳሾቹ ቀላል ሰዎች አይደሉም። ህዝብን ለጭካኔ ተግባር በማነሳሳት፣ ራሱን ለነሱ ስልጣን መጠበቅ ለቤተሰባቸው መልካም ህልውና ማረጋገጥ የራሱን ቤት አፍርሶ፣ ልጆቹን በትኖ ያለ ቀባሪ በየጉድባው ተረፍርፎ ይቀራል። ከሁለት አስርት አመታት በፊት የንጋቱ የቅዳሴና የወንጌል ትምህርት መሃል ላይ አስገብቶ እስካሁን ድረስ የማይረሳኝ አባባል የተናገረ አንድ ቄስ ንግግሩን አሁን ካለው ሁኔታ ጋር ሳገናዝበው ግርምት ፈጥሮብኛል። ቄሱ ፍካሬ እየሱስን ለምእመናኑ ሲያስረዳ እንዲህ አለ:- “ህዝብ በህዝብ ላይ ይነሳል፣ አማራው በኦሮሞ፣ ትግሬው በአማራው፣ አማራው በትግሬው ላይ ይነሳል”። ቄሱ የራሱ ምሳሌ መስጠቱ ነበር እንጂ እየሱስ ስለ ትግሬ፣ አማራና ኦሮሞ ያለው ነገር አይኖርም። እንግዲህ ማርያም ሰሜን ሸዋ መጥታ ከርማለች፣ ፅላተ ሙሴ ጣና ደሴት ላይ ይገኛል፣ የክርስቶስ መስቀል ግሸን ላይ ተቀምጧል የሚሉ አይን ያወጡ ተረቶች በሃይማኖት ሰዎች ስለሚነገሩ ፍካሬየሱስ ውስጥ ስለ ኦሮሞ፣ አማራና ትግራይ የተፃፈ አለ ቢሉም አይከለከሉ። ዳግማዊት እየሩሳሌም በኢትዮጵያ አለች ይባልስ የለ? ምን ይሳናቸዋል? የሚያሳዝነው “እውነት እውነት” እያለ ከንፈር የሚመጠው ምእመን ነው። እነሱ ይህን የሚያደርጉት የበላይነቱን ትርክት ስሜት ውስጥ በሚያስገቡ ነገሮች ለማጠናከር ነው። “ህዝብ በህዝብ ላይ ይነሳል” የሚል ሃይለ ቃል ቅዱስ ደብር ውስጥ ከተሰበከ ያሁኑ ጦርነት ስሩ የሚመዘዘው ከአቢይ ሶስት አመት ሳይሆን ቀደም ያለ ዝግጅት እንዳለ ፍንጭ የሚሰጥ ነው። እኔን የሚመስለኝ አቢይ ለዚህ እቅድ የገበጣ ጠጠር እንደተደረገ ነው። ሰው ሁሉ በአቢይና ኢሳያስ ላይ ይረባረባል። እርግጥ ነው ሁለቱም በትግራይ ላይ የየራሳቸው አውዳሚ የሆነ የግል አጀንዳ አላቸው። ገዢና ሻጭ ገበያ ላይ በሚገባ ተገናኝተዋል። ሁሉም በሌላው ላይ አትራፊ ናቸው። ነገር ግን ማንንም ግለሰብ የሚያነሳውና የሚያገነው ስርአት አለ። ስርአቱ ግን ሲመታ እንጂ ሲተኩስ አይታይም። የሚታዩትና የሚረገሙት ግለሰብ ተዋናዮቹ ናቸው። ግለሰቦቹ ሲሄዱ ሌላ ይተካል። የ100 አመት አሃዳዊነት ብን ብሎ አይጠፋም። እንዲያውም እጅግ በተማረ ግን በተግባር መሃይም በሆነ ትውልድ ተጠናክሮ ቀጥሏል። አቢይ በልደቱ ወይም በእስክንድር ቢተካ አሃዳዊነት የት ይሄዳል? ልዩነታቸው አቢይ አሃዳዊነትን ማክረሩና ልደቱና እስክንድር ግን አለዝበው ስለሚይዙት ብቻ ነው። ልዩነታቸው የሜቶዶሎጂ ልዮነት ነው። ለሶስቱም የፌደራል ህገ መንግስቱ ከትግራይ የመጣባቸው መቅሰፍት አድርገው ያስባሉ። ቀሪዎቹ የህገ መንግስቱ ተጠቃሚ ክልሎች ደግሞ ወደ ትግራይ የተወረወረው ፈንጂ እንዳይነካቸው ጥግ ይዘው ከመቀመጥ በስተቀር እግራቸው ስር ጉድጓድ እየተማሰ ባለበት ሁኔታ በአርምሞ ተውጠው ወይንም ወደ ትግራይ ዘምተው የገዛ እጃቸውን በመቁረጥ ላይ ተሰማርተው ባሉበት አሁንም አሃዳውያንን ክልልነት እንዲሰጧቸው ይማፀናሉ!! አይ ትግራይ! ልፋትሽ ከንቱ! ነፃ ያወጣሻቸው ነፃነትሽን ሲገፉሽ! አንድ የአማራ ትውልድ የነበረው የአድዋ ገበሬ ነው አሉ የሰብሉን ነገር አይቶ እንዲህ ብሎ አንጎራጎረ:- “ታዘብኩሽ ማይ ጓጓ፣ ማድጋ ዘርቼስ ማድጋ?”። ትግራይ ልፋትዋና ሞቷ ትርፍም ባይኖረው የዘራችውን ብቻ እንኳ ብታገኝ ተመስገን ባለች! አሁን እኮ አዛዥ ማን እንደሆነ በግልፅ እያየን ነው። አቢይ ተሸንፎ ሰራዊቱን ከባሰ ውድመት ለማዳን ብሎ ከመቐለ፣ ከወልድያ፣ ከደሴ ቢያፈገፍግ “ከህወሓት ጋር መክረህ ጥለህላት ወጣህ” እያለ ቅጡ እስኪጠፋው ድረስ ያልተቆጣው የአማራ ልሂቅ አለ? ያቺን ለማካካስ ብሎ የትግራይ ሰራዊት በየለቀቀለት ሲዘምት ለጊዜው የነ ሃብታሙ አያሌው የቃላት ሜዳልያ ተሰጥቶታል። ሆኖም ግን “የትግራይ ሰራዊት ተመልሶ መቐለ ሲገባ እዛው እንገናኛለን” የተባለው ቀርቶ መገናኛው ነፋስ መውጫና ጪፍራ ሆኖ ሲገኝ ኢትዮ360 በአቢይ ላይ አማርኛውን ይቀይራል። እስቲ እውነት እንነጋገር። ኢትዮጵያን የሚያስተዳድረው አቢይ ነው ወይስ ኢሳት? የሚፈልጉትን ካደረገላቸው በኋላ በማግስቱ አብይን አውልቀው እንደሚጥሉት የማይገምት አለ? “በሬ ሆይ…”! ህዝብን በህዝብ ላይ በጥላቻ፣ በምሬትና በጭካኔ የምታነሳሳው አንተም የተናደድክና ያበድክ በመምሰል፣ ምግብ እንደማይበላልህ፣ ሳትተኛ እንደምታድር፣ ገንፍለህ ማይኩ በእርግብግቢት እስኪሰነጠቅ ድረስ እየጮህክ ድራማ እየተወንክ ነው። ባለሞያዎቹ እንደነ ታማኝ በየነ፣ አብራር አብዶ፣ “አብየ ይመር” ያውቁበታል፣ የነገው የደራ ገበያቸው የት እንደሚሆን ያውቁታልና። መቸም በርግጠኝነት ትግራይና ኦሮሚያ አይደለም እነሱ የተወኑበት ድራማ የሚታየው። ሙያ ሳይሆን የሚልዩን ብሮች ኮንትራት ያለባቸው የነ ኢሳቱ አንዳርጋቸው ግን የጄኖሳይድ ፕሮጀክታቸው ኪሳራ እንዳያስመዘግብ ስልት በሌለው ግልብነት “አረመኔ ሁኑ” እያለ ደም ስሩ እስኪገታተር ይጮሃል። የታማኝ ትወና ረቀቅ ያለች ናት። እንደ ማርቲን ሉተር በጭብጨባ ታጅቦ ንግግሩን በልዩ ቅላፄ ይቀጥላል። በውጊያ እሳት ላይ ያሉት እንደነ ጀኔራል ታደሰ ወረደማ ረጋ ብለው ሰራዊታቸውን ሲያናግሩ ማየት ነው። ለካ እውነትም ባዶ ቆርቆሮ ሲንከባለል ይጮሃል፣ ሲሞላ ግን ድምፅ የለውም። ታማኝ እንደሆነ ከመሸበት አዳሪ ነው። ወጣት የመድረክ አስተዋዋቂ ሆኖ ሻለቃ መላኩን ሲያሞጋግስ ኖሮ ሰሞኑን ደግሞ በሰይፉ ቀርቦ “ኢህአፓ ሆኜ ለመታገል ሳይሳካልኝ ቀረ” እያለ አይኑን በጨው አጥቦ ያሁኑን ትውልድ ያጭበረብራል። በኢህአፓ ሺ ወጣት ያለቀበት ጎንደር ታማኝን አፉን ከፍቶ ሲሰማና ሲያጨበጭብለት ማየት የህዝብም ወስላታ አለው ለካ ያሰኛል። እርም የሌለው የጎንደር ዳያስፓራ ሻለቃ መላኩን አመስግኖ የለ? ወደ አሜሪካ ስላባረረው! ይብላኝ በመላኩ ቀይ ሽብር እዚህ ሞቶ ለቀረው። ምን ይደረግ፣ አርባ አራት ታቦት መቁጠር ህሊናን አይፈጥር! ጎንደርን ከጥፋት አድናለሁ ብሎ ሱዳኖችን የጨረሰው አፄ ዮሃንስ ነበር። ታሪክን በሚፈትን ሁኔታ በጎንደሮች የተሳደዱትን የአፄ ዮሃንስ ሰራዊት የልጅ ልጆች ተቀብለው ያስጠለሉት ሱዳኖች ናቸው። “ከአማራ ሱዳን ይሻለኛል” አለ ደብረፅዮን ተብሎ እንደ ወንጀል ተቆጠረ፣ ስታሊን ገብረ ስላሴም ለማስተባበል ትግል አደረገ። ቅን ሰው ስለሆነ ይሉኝታ ይዞት ነው! ግን ለምን? ከአስርቱ ቃላት የማልቀበለው ነገር ቢኖር “ጠላትህን ውደድ” የሚለውን ነው። “አትግደል” የሚለውን ተቀብየ ጠላቴን ባልገድለውም እንድወደው ግን ግዴታ የለብኝም። ክርስቶስ “የሚሰሩትን አያውቁምና ይቅር በላቸው” ብሎ ለአባቱ ምህረትን ለመነላቸው፣ ላሰቃዩትና ለሰቀሉት ሁሉ። እኔ ግን ተራ ግለሰብ ነኝ እንጂ ክርስቶስ አይደለሁም። ሳያውቅ በስህተት ሳይሆን ሆን ብሎ በእብሪት የሚጎዳኝን ይቅር አልልም። ተው ሲባል ለሚስቅና ለሚያላግጠው ምህረት ይገባዋል? ትግራይ አልጠፋለት አለች እንጂ ብትጠፋለት ኖሮ ዘላለም ጀግንነቱን እየቆጠረ ይኖራል፣ ይፀፀታል ተብሎም አይታሰብም። ለክርስቶስ እጅግ የቀረቡት የትግራይ የኦርቶዶክስ ሃይማኖት መሪዎች እንኳን “…ይቅር በላቸው” አላሉም ራሳቸውን ክፉ መንፈስ ከተጣናውታቸው ሰዎች መራቅን መረጡ እንጂ። ቆረንጦስ 6:17 ላይ እንዲህ ይላል:- “እግዚአብሄር አለ:-“ከመሃላቸው ውጣና ለብቻህ ሁን፣ ንፁህ ያልሆነውን አትንካ፣ እናም እቀበልሃለሁ”። ትግራይ በኢትዮጵያ ውስጥ ከአማራ ጋር አብራ ለመቆየት ብትወስን እንኳ እንደተፋታ ባልና ሚስት ተኳርፈን እንኖራታለን እንጂ ፍቅር የሚባል አይታሰብም። ስላልጠፋን ነው የተሰራውን ይህ ሁሉ ጉድ የምንረሳው? የጠፉትስ? ካርታ ላይ ያለው የኢትዮ-ሱዳን ድንበር የፓለቲካ እንጂ የፍቅር ድንበር አይደለም። የፍልስጤሞች ወዳጅ የሆነችው ያስጠለለች እናታቸው ዮርዳኖስ ናት ወይስ ያባረረች እስራኤል? ታየኝ ፍልስጤሞችና እስራኤሎች ዮርዳኖስን እንደ ባእድ ቆጥረው እርስበርስ ሲዋደዱ! እንዴት ነው አይናችን እያየ “ከሱዳን አማራን እወዳለሁ” የምንለው? እነሱ “ከሱዳን ጋር አንዋጋም ወንድማችን ነው፣ ከትግራይ ጋር ግን እስከመጨረሻ ነው” ያሉበትን ቪድዮ ስታሊን ብትፈልገው ጥሩ ነው። አማራ “ሱዳን ወራኛለች” እያለ ግን ደግሞ “ወንድም ህዝብ ነው” ካለ፣ የትግራይን ህዝብ አንድ ፐርሰንት ያስጠለለችው ሱዳን የትግራይ ወንድም የማትሆንበት ምክንያት ይነገረን። ነፍሰ ጡር እያለች በፋኖ የተንገላታችው ሁመራዊት የሱዳን ድንበርን በእግር አቋርጣ ስትሄድ ያየ ባለ አህያ ሱዳናዊ እሷን አህያው ላይ ጭኖ ወደ መጠለያ ወሰዳት ስሰማ እምባየ ወረደ። ይህን አርጅቼ ራሴን እስክረሳ ድረስ አልረሳውም። ካርቱም እንድ ሳምንት ያህል ቆይቻለሁ። ድሮም በልጅነት የአል ፈናን መሓመድ ወርዲ ዘፈን ደሜ ውስጥ ገብቶ ነበርና ሱዳን ሲባል በርተው ይታዩኛል። የካርቱም ጉብኝቴም የነበረኝን ስሜት የሚያጠናክር ነበር። ሱዳንን አትውደድ ከምትሉኝ አርባ ጅራፍ ግረፉኝ። የስሜት መነካት እንጂ የቆዳ መላጥ አያምም። ምጥ የሚረሳው ህመሙና ጉዳቱ ልጅ ስላስገኘ ነው። ለዚህ ነው እናቶች ሌላ ምጥ የሚመኙት። የትግራይ ጉዳት ምጥ አይደለምና አይረሳም። ትግራይ ያተረፈችው ውድመት እንጂ ልጅ አይደለም። ልጆቿንማ በገፍ አጣች እኮ! ህዝብ በህዝብ ላይ እንዲነሳ ብቻ ሳይሆን በክፍተኛ የጭካኔ ስሜት እሳት ለብሶ እሳት ጎርሶ እንዲዘምት የሚያስችለው አንዱ ዘዴ እንዲጠቃ የተፈለገው ህዝብ በአርአያ ስላሴ የተፈጠረ የሰው ፍጡር ሳይሆን ለሰው ልጆች ጠንቅ የሆነ ነገር አድርጎ በማቅረብ ነው። ሰው ለሰው ማዘኑና ርህራሄ ማሳየቱ አይቀርም፣ ለአውሬ ግን ያለውን አቅም ተጠቅሞ ያጠፋዋል እንጂ ዝም ብሎት አያልፍም። ጅብ ከሰፈር ገባ ከተባለ ህፃን ሳይቀር በስሜት ተነስቶ በጡጦውም ቢሆን ጅቡን ሊመታ ያስባል። “እረ ተውት፣ ፍጡር ነውኮ” የሚባልን ፍልስፍና የሚሰማ የለም። ትግራይ “የቀን ጅብ ነው” የተባለ ጊዜ መቸም ትግራዋይን በአካል አይቶ የማያውቅ ሰው ሁሉ በተለምዶ በሩን ዘግቶ ከተኛ በኋላ የሚመጣው ሳይሆን “በቀን የሚመጣማ እጅግ አደገኛው” ነው ብሎ የሚያስብ ሰው ጅቡ ሳይቀድመው ለመቅደም ይሞክራል። ከሰፈር የትግራይ ልጆች ካሉም “አሃ! አብሮኝ የሚማረው ያያ ሓጎስ ልጅ ለካ ጅብ ነው” ብሎ ልጅ እናቱን ሊጠይቅ ይችላል። እናቲቱም የቆየ የዘር እብደት ካለባት “አዎ ጅብ ነው፣ እንዳትጠጋው” ልትለው ትችላለች። ይህ ልጅ ሲያድግ ፋኖ ይሆንና የትግራይ ልጅ ሲያገኝ ገድሎ ያቃጥላል ወይንም ወደ ወንዝ ይጥላል። ካንሰር አለብህ የተባለ ሰው ከውስጡ አስቆርጦ ለማስወጣት የብዙ ሺ ብር ወጪ ያወጣል። ካንሰሩ ሰው ሆኖ ከፊቱ ካየው ብር ሳይከፍል ያጠፋዋል። ከአረም የሚመለስ እጅስ አለ? እህል አጥፊ ነው፣ ያስርባል። ሰው የመሰለ አረምም በመጎልጎያ ሳይሆን በዲሞፍተር ይነቀላል። “የትግሬ ደም ቢኖረኝ በሲሪንጋ መጥጬ አወጣው ነበር” ይላል አንዱ (በምን እድሉ ያገኘዋል እንጂ! (ሳቅ በሳቅ)። ሌላው የተነካ ደግሞ “የትግራይን ህዝብ ጋዝ አርከፍክፈው ለምን አያቃጥሉትም?” ብሎ ይጠይቃል። ካምፕ ፋየር መሆኑ ነው! (ሳቅ በሳቅ)። “አምላኬ ሆይ የሚበላ ከልክለኝ እንጂ ከደንቆሮ ጋር አታውለኝ” ብሎ መማፀን ያስፈልጋል። ዘረኛ ፕሮፓጋንዳ እንዲህ አይነቶችን ሰዎች ነው የሚያመርተው። ለትግራይ ህዝብ የወጡለት ሰብአዊ ፍጡርነቱን የሚነፍጉ የቅፅል ስሞች ከመብዛታቸው የተነሳ መቁጠር አቁመናል። ሰዳቢዎቹ ግን ንዴታቸው ስላላቋረጠ በየሽንፈታቸው ማግስት አዲስ ስድብ ይፈለፍላሉ። “ከትግሬ ሰይጣን ይሻለናል” ያሉት በሃጥያት የተበከሉ ቄስ የተናገሩት ምን ትርጉም እንዳዘለ አልገባቸውም። የታያቸው አምርረው መሳደባቸው ነው፣ ወይ ቅስና! ከነሱ ሰይጣን ይሻላል ካሉ ከመላክና ሰይጣን ሌላ አማራጭ ስለሌለ ትግራይ መላክ ነው ማለት ነው! (ሳቅ በሳቅ)። ከሁሉም የሚገርመው የባጫ ደበሌ በትግራይ ህዝብ ላይ የሰነዘረው ሰብአዊ ፍጡርነትን የሚነሳ ስድብ ነው። “ዝንጀሮ ናቸው” አለ! በመልክ ከሆነ ሰው ይፍረድ፣ ዝንጀሮ የሚመስለው ሰዳቢው ነው ተሰዳቢው? ተሳዳቢው ሳይንስን ስላልተማረ ነው እንጂ ሰው ከዝንጀሮ አይደል የተገኘው? በዚህ አይነት ሉሲን ጁንታ ሳይላት አይቀርም። ብልግናን በብልግና መመለስ ተገቢ ባይሆንም “መስተዋት ቤት ውስጥ ሆነህ ቀድመህ ድንጋይ አትወርውር” ብሎ መምከር ግን ተገቢ ነው። ወታደር ሆኖ የማረከችውና ጄኔራል ያደረገችው ዝንጀሮ ምን ያህል ከሱ የላቀች ጀግናም ሊቅም የሆነች ዝንጀሮ ናት? ሲናደዱ አፍን መቆጣጠር አዋቂነት ነው። የትግራይ መሪዎች በጨዋነት ጠላታቸውንም ቢሆን በአደባባይ የማይዘልፉት እኮ ባህላቸው ከፍ ያለ ስለሆነ እንጂ ማንን ፈርተው? 2. ዲሂዩማናይዜሽን (ሰብአዊ ፍጡርነትን መንሳት) ዲሂዩማናይዜሽን ወይንም ሰብአዊ ፍጡርነትን መንሳት በአርመንያና አዘርባጂያን መካከል በነበረው ግጭት ውስጥ ከፍተኛ ሚና ነበረው። በጆ ነርሰስያን እንደተፃፈው አርመን ጠል የሆነው የአዘርባጂያን ፕሬዚደንት አሊየቭ ለስልጣኑ በህዝቡ ዘንድ ድጋፍ ለማግኘት ሲል የአርመንን ጥላቻ ያስፋፋ ነበር። የአርመን ህዝብን ከሰውነት ውጭ በማድረግ “ውሾች፣ ተባዮች” ናቸው ይላቸው ነበር። ማት ዳንኤልስና ዱግ ባንዶው ይህ በሽታ አሜሪካንም ሳይቀር እየነካካት መሆኑን ፅፈዋል። አንድ እንደ ቀልድ የሚነገር ነገር አለ። ሪፓብሊካኖች ዴሞራቶችን የሚመርጠውን ህዝብ “ዲመንክራትስ” (ሰይጣናዊ ገዢዎች) በሚል አጉል ቀልድ ይጎነትላሉ። “ይቺ ጥሬ ስታድር አትቆረጠምም!” ነው። ለነገሩ አሜሪካ ለእንደዚህ አይነት ታሪክ አዲስ አይደለችም። አፍሪካውያንን እንደ ማገዶ በጥምር በጥምር ጀልባ ውስጥ እያጨቁ የደረሰ ይድረስ ብለው አሜሪካ ድረስ ካጓጓዙ በኋላ እንደ በግ ወገባቸውን እያስጨበጡ፣ እንደፈረስ ጥርሳቸውን እያስፈተሹ ሲቸረችሩ አልነበር? ይህን ድርጊት አናቆምም ብለው ነበር እኮ ረዥም የእርስበርስ ጦርነት ያካሄዱት። በአስራ ስምንተኛው ክፍለ ዘመን በአሜሪካ የተካሄደ አንድ የባርያ ጨረታ ማስታወቂያ ፓስተር ሁለት አፍሪካውያን ወንድና ሴት ስእል ግራና ቀኝ ይታያሉ፣ በአገራቸው በክብራቸው እያሉ ባማረ አለባበስ የተሳሉበት ስእል። ነገር ግን ማስታወቂያው እንዲህ ይላል:- “የሚሸጥ! ዘጠና አራት በመልካም ጤንነት ላይ ያሉ የኒግሮዎች ካርጎ። እሁን በደረሰው በዚህ ካርጎ ሰላሳ ዘጠን ወንዶች፣ አስራ አምስት ጉብሎች፣ ሃያ አራት ሴቶችና አስራ ስድስት ልጃገረዶች ይገኙበታል።” እግዚአብሄር ያሳያችሁ “ካርጎ” ነው እኮ ያሏቸው። እንዲህ ተብለው ይገዙና የነጮች መጫወቻ ሲሆኑ ነበር። አቅም ስላልነበራቸው ብቻ ሳይሆን ጌቶቻቸው ከውሾቻቸው በታች አድርገው እያዩዋቸው ጭንቅላታቸውን ስላበላሹባቸው ራሳቸው የተሰጣቸውን ደረጃ በፀጋ ተቀብለው ከውሻና ከድመት በታች ሆነው የኖሩም አሉ። ነፃነት ሲሰጣቸው ነጮችን እንደ ባለውለታ የቆጠሩ ብዛት ነበራቸው። አሁንስ ቢሆን ህግ እየያዛቸው እንጂ በ21ኛው ክፍለዘመን “የጥቁሮች ህይወትም ህይወት ነው” ወይንም “ብላክ ላይቭዝ ማተር” እየተባለ አይደለምን? በቀጥታም ባይሆን የአሜሪካ ጥቁር ህዝብን እንደ ዝንጀሮ የመቁጠር ስሜት በስፋት ይንፀባረቃል። እንዲህ አይነቱ ስሜት በነሱ ላይ የሃይል እርምጃ ለመውሰድ የሚያበረታታ እንደሆነ አያጠያይቅም። በሮም ዘመን ሮማውያን ያልሆኑ በጨረታ ተሽጠው የግል ንብረት ይሆኑ ነበር። ይቺ በኢትዮጵያም በስፋት ተተግብራለች። የጠቆረውን “ባርያው” እያልን የምናቆላምጠው ከየት ያገኘናት ታሪክ እንደሆነች ይህ ትዉልድ ብዙም አይገነዘብም። በሃይል ከተወረሩት የደቡብ ኢትዮጵያ ሰዎች ተፈንግለው በመላ ኢትዮጵያ ተዘርተው እንደቀሩና እስካሁንም በህብረሰቡ ዘንድ ከሰው በታች ሆነው እንደሚታዩ ይታወቃል። ከአሜሪካ ሳንወጣ ቀይ ህንዶች ወይንም የአሜሪካ ህንዶች በሚባሉት ነባር ባላባት ህዝቦች ላይ በአውሮፓ ነጭ ሰፋሪዎች የተፈፀመው የዘር ማጥፋት ዘመቻስ የተጠቀመው ይህንኑን ሰብአዊ ፍጡርነትን መንሳት አልነበረም እንዴ! ይህን ጉዳይ በሚመለከት እውቁ የመብት ታጋይ ዶ/ር ማርቲን ሉተር ኪንግ በአንድ ወቅት እንዲህ ብሎ ነበር:- “አገራችን የተወለደችው በዘር ማጥፋት ነው። ይህም ሊሆን የቻለው እንደ በጎ ነገር ነባሮቹ አሜሪካውያን ህንዶች ከሰው በታች ናቸው የሚለውን አስተሳሰብ ተቀብላ በማራመዷ ነበር። በፓሊሲ ደረጃ ነባር ህዝብን በማጥፋት ከአለም አንደኛ የሆነው እኛ ነን። ይህ አሳዛኝ ድርጊትንም እንደ አገር ክብር ቆጠርነው። ስለሆነም ለዚህ አሳፋሪ ድርጊት ቁጭት የሚባል ነገርም አናሳይም፣ ይልቁንም በስነፅሁፍ፣ በፊልም፣ በድራማ፣ በተረት ስናሞጋግሰው እንታያለን።”
ቀይ ህንዶች የተባሉት የአሜሪካ ነባር ህዝቦች የአውሮፓ ስደተኛ ሰፋሪዎች ቤታቸው ድረስ ሄደው “ምህረት የሌላቸው አረመኔዎች” ይሏቸው ነበር። በኢትዮጵያ ውስጥም እንዲህ አይነት አይን ያወጣ ድፍረት ነበረ ባለፉት ሩቅ ዘመናት። ሰው በሆኑበት ወደ ቀያቸው ዘው ብለው በጉልበት ገብተው ነባር ኗሪዎችን ከሰው በታች አድርገው በመቁጠር ለሰላም ስንል የማንጠቅሳቸው አስነዋሪ የሆኑ በርካታ የቅፅል ስሞች፣ ተረቶች፣ ቀልዶች ተነግረዋል። አሁንም በሰፊው ጥቅም ላይ እየዋሉ ቢሆንም ነገር ላለማጫጫስ ስል ከመዘርዘር እቆጠባለሁ። አንዱን ብቻ ግን ነካ አድርጌ ልመለስ። የእውነት የተደረገ አይመስለኝም፣ ነገሩ ቀልድ ነው። ሆኖም ግን በህዝብ ላይ የሚያመጣው ምሬት ያው ነው። አንዱ ንጉስ አዋጅ ሲያስነግሩ “ሰው አትግደሉ ----ም ቢሆን”። በዘዴ ሰው አደለህም ማለት እንዲህ ነው። ወደ ቀይ ህንዶች ጉዳይ ልመለስና ሊማን ፍራንክ ባውም ከአውሮፓ ሰፋሪዎች አንዱ ያደረገውን የዘር ማጥፋት ቅስቀሳ እንዲህ አድርጎ ጠቅሶታል:-“የደህንነታችን ብቸኛ ዋስትና ቀይ ህንዶችን ጨርሶ ማጥፋት ነው። ስልጣኔያችንን ከአደጋ መጠበቅ የምንችለው እነዚህ ያልሰለጠኑና ሊሰለጥኑ የማይችሉ ፍጡሮችን ከምድረገፅ በማጥፋት ነው”። የዚህ ሰፋሪ ንግግር ቁርጥ የኢትዮጵያን ትመስላለች። ትግራይ የኢትዮጵያ ብቸኛ አደጋ እንደሆነችና ከምድረገፅ ጠፍታ ዘመናት ካለፉ በኋላ ተቆፍራ ብትገኝም ችግር እንደሌለው በዲያብሎስ ነው በዲያቆን ዳንኤል አለም እስኪደነግጥ ድረስ ባደባባይ ተናግሯል። ክትግራይ ሰይጣንን የመረጡት እነዚህ ድልብ ዘረኞች ዲያብሎስ ቢባሉ ይከፋቸዋል ብላችሁ ነው? ማት ዳንኤልስና ዱግ ባንዶው ሰለ ቻይናዎቹ ዊጊር ሙስሊሞች በስፋት ፅፈዋል። ቻይና “ምን ያለበት ዝላይ አይችልም” እንደሚባለው አንድን ህዝብ ለይቶ የሰው ፍጡርነቱን መካድ በተመለከተ የምትወስደው አቋም ከትልቅነቷና ከአብዮት ታሪኳ ጋር አይመጣጠንም። ቻይና ዋናዋ የሰው መብት ገፋፊ አገር ናት። ዚንጅያንግ በሚባለው ክፍለ ግዛቷ ውስጥ አንድ ሚልዮን የዊጊር ሙስሊሞችን የምታጉሩባቸው ግዙፍ ካምፓች ገንብታለች። ካምፓቹ “የተሃድሶ ካምፓች” (ሪ-ኢዱኬሽን ካምፕስ) ይባላሉ። የሚያስደምመው ነገር ግን ለነዚህ የተሃድሶ ካምፓች የተቀጠሩላቸው መምህራን ሳይሆኑ የተገዙላችው የሚከተሉት ናቸው:- 2768 የፓሊስ ዱላ፣ 550 የከብት ማገጃ የኮሬንቲ ጉጦች፣ 1367 የእጅ ማሰሪያ ካቴና፣ እንዲሁም 2792 አድማ በታኝ የበርበሬ መርጫ ጣሳዎች ናቸው። ኢትዮጵያ የቻይና ጎበዝ ተማሪ ሆናለች። ይህን ይህን ከቻይና ሌላ ሌላው ደግሞ ከኤሪትርያ። ቀድማ የተፈጠረች አገር ተማሪ ሆና ቀረች። በጎ በጎውን መማር እንኳን ያባት ነበር፣ ክፉ ክፉውን በመቅሰም ከክፍሏ አንደኛ ሆናለች። በበጎ ነገር መታወቅ “በጁንታው” ዘመን ቀረ! ቻይና ጥሩ ጓደኛ አግኝታለች። ሁለት ሆኖ አይፈራም። ቻይና ዊግርን አጉራ ትቀጠቅጣለች ኢትዮጵያ በርካታ ካምፕ ፈጥራ ተጋሩን ትቀጠቅጣለች። መቸም ትግራዋይን እንደ ሰው የሚያይ መንግስት እንደ ድመት በቀን አንድ ዳቦና አንድ ጉንጭ ዉሃ ብቻ አይሰጥም። ተጋሩ ጅቦች፣ ሰይጣኖች፣ አረሞች፣ ካንሰሮች፣ የልጆች ማስፈራሪያዎች፣ ሽብርተኞች፣ እየተባሉ በኢትዮጵያ ህዝብ አእምሮ ውስጥ ስለተሳሉ እየታፈሱ ነው፣ እየተሰቃዩ ነው ሲባል ሰው ስሜት እየሰጠው አይደለም። መንግስትም ፕሮፓጋንዳው እንደሰመረለት አይቷል። የህግ ሰዎችም የሰዎች እንጂ የጅቦች ህግ የለንም ብለው ነው መሰል ፀጥ ብለዋል (ሳይወዱ ሳቅ በሳቅ!)። ስለዊጊሮች ከሰው ያነሱ መሆንን በሰው አእምሮ ለመቅረፅ በየቦታው የተለጠፉ ትልልቅ ፓስተሮችና የግድግዳ ላይ ምስሎች አሉ። ቢቢሲ ካሰባሰባቸው ከብዙ በጥቂቱ ከዚህ ቀጥሎ ያሉት ምስሎች ይገኙባቸዋል። አንደኛ:- አንድ ሰው መጥረጊያ ይዞ ከመንገዱ ላይ ያገኛቸውን የጥቃቅን ዊጊሮች ክምር ጠርጎ ሲያስወግድ የሚያሳይ፣ ህለተኛ:- የኮንክሪት ማስተካከያ ዳምጠው ዊጊሮችን ጨፍልቆ ከስሚንቶው ጋር ሲደመድማቸው የሚያሳይ፣ ሶስተኛ:- ዊጊሮች ምስላቸው ጥቃቅን እንደሆኑ ወይንም ጥቁር እንደሆኑ ተደርገው ይሳላሉ። ቻይና ይህን ጉድ ይዛ ነው የተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብት ቻርተር ከዋና “ጠባቂዎች” አንዷ ሆና የተቀመጠችው። ድንቄም! የኢትዮጵያ መሪ ጄኖሳይዲስቶች መሃይም አይደሉም። እስኪግሉ ድረስ የተማሩ ናቸው። “ኩሉ እመክሩ ወዘሰናይ አፅንኡ” በሚለው መርሆ ስር ተምረው “እንኳን ደስ ያላችሁ” ተብለው የተመረቁት ለካ ሰናይ ሰናዩን አይደለም። የነሱ መርሆ “ኩሉ እመክሩ ወዘጄኖሳይድ አፅንኡ” የሚለው ነው። ይህ ባይሆን ኖሮ እንደ አሪስቶትልና ሶቅራጦስ ለሰው ልጅ የሚበጅ የፍልስፍና ትምህርት ተምሮ ዶክትሬት ዲግሪ የበጠሰው ዳኛቸው አሰፋ ራሱ እንደ ሳቬጅ አድርጎት በአደባባይ ትግሬን እየፈለግህ አጥፋ ይል ነበረን? በናዚው የአይሁዶች ፍጅት ዘመን ሰብአዊ ፍጡርነት የመንሳት (ዲሂዩማናይዜሽን) ከፍተኛ ደረጃ የደረሰበት ነበር። አሁን ስለራሴ ህዝብ በተመሳሳይ ጉዳይ ስፅፍ ከልብ እያዘንኩ ነው። በርሊን አጠገብ፣ ኦራንየንቡርግ ቀበሌ ውስጥ የሚገኘው የሳክሰን ሃውዘን ማጎርያ (ኮንሰንትሬሽን) ካምፕን ከእግር እስከራሱ ውስጥ ገብቼ ጎብኝቸዋለሁ። በሳጥን የሞላ የሰው ጥርስና በሰው ቆዳ የተሰራ የገንዘብ ቦርሳ ሚዩዝየሙ ውስጥ አይቻለሁ። እስረኞችን ገድለው ለማቃጠል የሚከቱባቸው ትልልቅ ምጣዶችን አየሁ። አጥንታቸው ተለቅሞ ለካልሲየም ማዳበሪያ ፋብሪካ በግብአትነት እንደሚሸጥም ተነግሮኛል። ጫማ ፋሪካዎች የጫማ ጥንካሬ የሚለኩባቸው እስረኞ ከቁጥራቸው በታች ጫማ ለብሰው በዛ ረሃብ 20ኪሎ አሸዋ ተሸክመው 20 ኪሎሜትር ዙር የሚሄዱበት አደባባይ አለ። ብዙዎች በዙሩ ላይ ይሞቱና ወደ ምጣዱ ይወሰዳሉ። በእስረኞቹ መከራ የናዚ ኤስ ኤስ ፓሊሶች ቢዝነስ ይሰራሉ። አዲስ አበባም እኮ ጁንታ ነህ ብለው ያሰሩትን ለመፍታት ፓሊሶች ብር እንደሚቀበሉ ይሰማል። ትንንሽ ኤስ ኤሶች! ህወሓትን ሊያዳክሙ አስረው በብር ይለቃሉ! ይህን የሚያደርጉት የሚያስሯቸው ተጋሩ ንፁህ መሆናቸውን በሆዳቸው ስለሚያውቁ ብቻ ሳይሆን ከሆዳቸው በስተቀር ሰለ ህወሓት ሆነ ብልፅግና ግድ ስለሌላቸው ነው። አይሁዶችስ ምንም ሳይበድሉ እይደል የተገፈፉት! ሃብታቸው ተዘርፏል የጥርሳቸው ወርቅ ሳይቀር ተነቅሏል። የሚገርመው ነገር ሳክሰን ሃውዘን ማጎርያ ካምፕ በር ስትደርስ የምታየው ከብረት የቀረፀ መልካም ምኞት አለ። ጄኖሳይዲስቶች ከሰው በታች ባደረጉት ላይ ምን ያህል እንደሚያሾፉ የሚያመለክት ፅሁፍ ነው። እንዲህ ይነበባል:- “አርባይት ማኽት ፍራይ”። ትርጉሙ “ስራ ነፃ ያደርግሃል ነው”። አስጎብኝዎቹ የነገሩኝ እንዲህ ነው:- እስረኞቹ የበሩን ፅሁፍ አይተው ተስፋ አድርገው ከገቡ በኋላ ፓሊሶቹ ለብስበው “መውጫችሁ የገባችሁበት በር ሳይሆን ምጣድ ቤቱ አናት ላይ የምታይዋት ጢስ መውጫ ናት” ይሏቸው ነበር። በጥይት መግደሉ ከአቅማቸው በላይ ሲሆንባቸው ሻወር ውሰዱ እያሉ መርዝ ጋዝ ከሚረጭበት ድፍን ቤት ውስጥ አስገብተው ይፈጇቸው ነበር። ጉብኝቴን ስጨርስ አእምሮየ ተቃውሶ ስለነበረ እኔም በጢስ መውጫው የምወጣ መስሎ ተሰማኝ። ሰዎች በሌሎች የሰው ልጆች ላይ እንዴት እንዲህ ደመ ቀዝቃዛ ይሆናሉ ከተባለ ስልታዊ ፕሮፓጋንዳ የአእምሮአቸውን ጤናማ ተግባር በማወክ ሊቆጣጠሩት የማይችሉት የሆነ የስሜት መመሳቀል ስለሚፈጥርባቸው ነው። ዛር ለአጭር ጊዜም ቢሆን ያመኑበትን ሰዎች ተቆጣጥሮ የእሳት ፍም ሳይቀር እንዲጎርሱ ያደርጋቸዋል። ባላምንበትም ይህ ራሴ በአይኔ ብረት ያየሁት ነው። በውኑ እሳት የሚጎርስና ወንድሙ የሆነው የአገሩን ልጅ ትግራይ ተወለድክ፣ አባትህ ትግሬ ነው እያለ ቁም ስቅል ያሳያል? ተይዞ ነው እንጂ! እኔን! ናዚዎች አይሁዶችን “አይጦች” ይሏቸው ነበር። አይጥን የሚወድ አለ? ሊገድል ዱላ የሚፈልግ እንጂ። ዴቪድ ሊቪንግስተን ስሚዝ እንደተረከው ሂትለርና ተከታዩቹ አይሁዶችን “ክብር ላለው የአለም ህዝብ ህልውና ከፍተኛ አደጋ የሚጋርጡ፣ ዝነኛ የሆኑ የስልጣኔ ጠላቶች ናቸው” ይሏቸውና የበሽታ አስተላላፊ እንደ ትል፣ ቅማልና ባክቴርያ እያደረጉ ይስሏቸዋል። ዴቪድ ሊቪንግስተን ስሚዝ የጠቀሰው የሂትለር የ1943 እ.ኤ.እ. ንግግር ይኸው:- “ዛሬ፣ አለም አቀፍ አይሁድነት የህዝቦችና መንግስታት መቡካትና መበስበስ መንስኤ ነው፣ ልክ ጥንትም እንደነበረው። ህዝቦች ይህን ቫይረስ ለማጥፋት የሚያችላቸው ጉልበት ካላገኙ እንደነበር ይቀጥላል።” ናዚዎች ጠላቶቻቸው የሆኑት ሁሉ የአለም አቀፍ አይሁዳዊነት አካላት እንደሆኑ እርግጠኛ ሆነው ይናገሩ ነበር። የሩስያ፣ የእንግሊዝና የአሜሪካን መንግስታት የተቆጣጠሩት አይሁዶች ናቸው የሚል እምነትም ነበራቸው። ይህ ማለት አይሁዶች ጀርመናውያን ቢሆኑም የጀርመን ጠላቶች ናቸው ተብለው ተፈርጀዋል። ታድያ የጀርመን ሰው እንዲህ ያለ አሳሳች ግን አደገኛ ፕሮፓጋንዳ እየሰማ ስለቀወሰ አይሁዶችን እንደ ሽንኩርት ቢከትፋቸው ምኑ ያስገርማል? “ተጋሩ ከኢትዮጵያ የዘመናት ጠላቶች ከሆኑት የውጭ መንግስታት ጋር አብረው አገራችንን ሊያጠፏት ነው” ተብሎ በፓለቲካ መሪው፣ በጳጳሱ፣ በፓስተሩ፣ በሙፍቲው፣ በፕሮፌሰሩ፣ በአገር ሽማግሌው፣ በሚድያው ነጋ ጠባ ሃያ አራት ሰአት ሲለፈፍ የኢትዮጵያ ህዝብ ለመጠራጠርና ለማጣራት አቅምም ፍላጎትም ይኖረዋል ተብሎ ይታሰባል? ሂትለር አይሁዶችን አይጥና ባክቴርያ እያለ በሚልዮኖች እየፈጀ አይሁዶችን እንግሊዝ፣ ራሽያና አሜሪካ ጋር አብረውብኛል እያለ በአገር ክህደት ይከሳቸው ነበር። አይሁዶችን ያመናቸው ጀርመናዊ እንዳልነበረ ሁሉ ተጋሩንስ ማን ይመናቸው? እዚህም እንደ ጀርመኑ የትግራይን ህዝብ በጉሮሮው ይዘው በረሃብ እየፈጁት ነው። “ተጋሩ ከአሜሪካ ጋር ሆነው ሊያጠፉን ነው” እያሉ በብልጠት ያማርራሉ፣ “ጣልቃ ገብነት ይበቃል” እያሉ የአሜሪካ አደባባዮችን ያጥለቀልቃሉ። “አያ ጅቦ ሳታመኻኝ ብላኝ” አለችው አሉ አህይት ጅብን፣ ከታች እየጠጣች አደፈረስሺብኝ ስላላት። የኢትዮጵያውያንን በተጋሩ ላይ የጀመሩት እብደት አለም እንዲጋራቸው ይፈልጋሉ ብቻ ሳይሆን ሊያስገድዱም ይሞክራሉ። አለም የጤና ጥበቃ መሪዋ ማን ሊሆን እንደሚገባ ደፋሮቹ ኢትዮጵያውያን እየነገሯት ነው። ኢትዮጵያን አሁን ማን ይሰማታል? አለም ከአዲስ አበባ ሸሽቶ ናይሮቢ እየሰፈረ! የራሷን ዜጋ ከአለም አቀፍ ተቋም አመራር ይልቀቅ የምትል አገር! ማርስ ላይ ተደርጎ ይሆናል እንጂ በምድርስ አልሰማንም። አለምን ያሸበረው ኮቪድን የተጋፈጠ ጀግና አማራ መሆን ነበረበት ለካ! ጊነስ ቡክ ኦፍ ሬከርድስ መቸም ይህንን ጨምላቃ ክህደት አይመዘግብም። በሩዋንዳው ጄኖሳይድ ሁቱዎች በገጀራ ሲጨፈጭፉ የነበሩት ሰውን ሳይሆን በረሮዎችን ነበር የሚፈጁት። እዚህስ እያለቁ ያሉት ተጋሩ ናቸው እንዴ? ጁንታ ወይም ካንሰር ወይም ጅብ ወይም ሰይጣን ናቸውኮ! ወይ ጉድ! “ምን አይነት ዘመን ነው ዘመነ ድሪቶ” አለ ድምፃዊ ተሾመ ደምሴ። የኛው ጄኖሳይድ ሳይጀመር ሩዋንዳ ኪጋሊ ተጉዤ ነበር። ስለ ሩዋንዳ እልቂት በወቅቱ በዜና እከታተል ስለነበርና አንድ ሁለት ፊልሞችም አይቼ ስለነበር ከኤርፓርት ወደ ከተማ ለመሄድ ስጋት አድሮብኝ ነበር። ሰአቱ ሌሊት ስለነበረም ጭምር ነው። በታክሲ ስጓዝ መንገድ ላይ ሬሳ ተረፍርፎ የማይ ይመስለኛል። በሰነበትኩባቸው በርካታ ቀናት የኪጋሊን አስድናቂ ውበት ላይ ማተኮር አልቻልኩም። የጄኖሳይድ መዘክሩን ለመጎብኘት ሄጄ ሰአቱ አልነበረምና ተዘግቷል ብለው መለሱኝ። አምላኬን አመሰገንኩ፣ በሺዎች የሚቆጠሩ የራስ ቅሎች አይቼ ስባንን ከማደር ዳንኩኝ። በማግስቱ ታላቅ በጎ ስራ ወደተሰራበት ሆቴል ሩዋንዳ አመራሁ። በጣም ያምራል። ድራፍት አዝዤ ቆምኩኝ፣ የቁም መደገፊያ ነበራና ጠረጴዛው። ሆቴል ሩዋንዳ የተባለው ፊልም ላይ ያየሁት ነገር ጋር እያስተያየሁ ድራፍቴን ጨርሼ ልቤ እንደተወጠረ ከግቢው ወጣሁ። የትግራይ ሆቴሎች አንድ ቀን ሆቴል ሩዋንዳ ይሆናሉ ብየ ግን በፍፁም አላሰብኩም። ከማድርበት ሆቴል አስተናጋጅ የሆነ ቱትሲ ኢትዮጵያዊ መሆኔን ሲገነዘብ ደስታውን ገለፀ። “ካገርህ ሚስት ፈልግልኝ” አለኝ። እኔም የውሸት ቃል ገባሁለት። የእውነት እንኳን አልሆነ። መቸም አንዷን ዘመዴን ነበር የምድርለትና ጁንታ ተብላ ሚስቱ ስትታሰር እሱ መግቢያ የት ይሆን ነበር?
ህዝብ በህዝብ ላይ ለምን እንደዚህ አምርሮ ይነሳል? ብየ ስጠይቅ “ፍካሬ እየሱስ ስለሆነ” እንዳትሉኝ። እሱንም ያልሆነ ስም ሰጥተው የሰቀሉት የራሱ ወገኖች ናቸው። አይሁዶች መልካም ነገር ያስተማረውን ክርስቶስን ምን ሲሉ አምርረው ጠሉት? ዴቪድ ሊቪንግስተን ስሚዝ የሰዎች ስሜት ተበላሽቶ ሌላውን ህዝብ እንደ አውሬ ያለ ርህራሄ ከመቀጥቀጥ የማይመለሱበትን ስነ አእምሯዊ ሁኔታ ላይ የጥናት ውጤቱን አቅርቧል። እንደ ስሚዝ ጥናት እንዲጠቁ የተፈለጉት ህዝቦች የሰው ልጆችን አስተሳስሮ ከያዘው የሞራል መብትና ግዴታ ስርአት ውጪ እንዲሆኑ ሲደረግ ነው። የተወሰነ ህዝብን ቀሪው ሁሉ ከሚጋራቸው ከሞራል እሴቶች እንዲገለል ከተደረገ በሱ ላይ የከፋ እርምጃ መውሰዱ አድራጊውን የሚያሸማቅቅ አይሆንም። ለዚህም ነው የማህበረ ሰብ የሞራል እሴቶች ስልታዊ በሆነ በረቀቀ እንዲሁም ተከታታይና ሁሉን አቀፍ የሆነ የማግለል ዘመቻ ለዘር ማጥፋት አመቺ ቅድመ ሁኔታዎች ሆነው የሚገኙት። በትግራይ ህዝብ ላይ እየተካሄደ የቆየውና አሁንም ተባብሶ የቀጠለው ጄኖሳይድ ዘርፈ ብዙ ነው። መነሻውም እንደሌሎች በአለም ላይ እንደተከሰቱት ዘር ማጥፋቶች በተጠቂው ማህበራዊ የበታችነት የወለደው ሳይሆን በተቃራኒው የተጠቂው የትግራይ ህዝብ ማህበራዊ የበላይነትን ለማውደም የሚደረግ ዘመቻ ነው። ይህ ለአለም የጄኖሳይድ መንስኤ ታሪክ ውስጥ አዲስ ክስተት ነው። የትግራይ ህዝብ ቁጥሩ ከእጥፊዎቹ ጋር ሲነፃፀር አናሳ ቢሆንም በአለም ላይ ገናና ከነበሩት ስልጣኔዎች አንዱ የሆነው የአክሱም ስልጣኔ ባለቤት ነው። አለን ከሚሉት የክርስትናና የእስልምና ዘመናዊ ስልጣኔዎች እጅግ ቀድሞ ጥልቀትና ስፋት ያለው የክርስትናና እስልምና ባህል የገነባ ህዝብ ነው። ጀግንነቱና የውግያ ስልቱም በተፈጥሮ ልቀት ያለው ከመሆኑ የተነሳ ኢትዮጵያን ከውጭ ወራሪዎች ሲታደግ የኖረ አርበኛ ህዝብ ነው። የአፍሪካ ብቸኛውን ፊደል የቀረፀና የፀሎትና የመወድስ ዜማዎችንም የፈጠረ በስልጣኔ የመጠቀ ህዝብ ነው። በርካታ ዘመናዊ ትምህርት የተማሩ የትምህርትና የኢኮኖሚ ልሂቃን ያሉት ሲሆን በወታደራዊ ዘርፍም በአለም ደረጃ በሚመደቡ ምርጥ የጦር ሊቃውንት የታደለ ነው። የተፈጥሮ ሃብት ውስኑነትና የአየር ንብረት ጫና ያለበት ቢሆንም ችግርን ተቋቁሞ የመውጣት አቅሙ እጅግ ከፍተኛ ነው። ለዚህም ነው ለዘመናት የደረሱበትን አሁንም በከፋ ሁኔታ ያጋጠሙትን አውዳሚ የሆኑ የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ አደጋዎችን ተአምራዊ በሆነ ጥንካሬ ተቋቁሞ የወጣና እየወጣ ያለ ህዝብ ለመሆን የበቃው። ብዙ የአለም ህዝብ ጠፍቶ ወይም እጅግ ተጎድቶ በቀረባቸው ጥፋቶች የትግራይ ህዝብ ግን አፈር ልሶ መነሳት የዘወትር ልማዱ ነው። የራሱን መብት አያስነካም የሌሎች ህዝቦች መብትንም አለመንካት ብቻ ሳይሆን በተቆርቋሪነት የሚቆምና ደሙንም እስከማፍሰስ የሚደርስ ታላቅ ህዝብ ነው። የዘር ማጥፋት ጉዳይ ሲነሳ በእንደዚህ አይነት ልቀት ባለው ህዝብ ላይ የመፈፀሙ ነገር የተለመደ አይደለም። ንቀት ዘር ማጥፋትን ይወልዳል፣ የትግራይን ህዝብ ሊንቅ በሚያስችለው የማህበራዊ ልቀት ደረጃ ላይ የሚገኝ ሌላ ህዝብ ለመኖሩ የሚታወቅ ነገር የለም። የሆነው ግን ይኸው ነው። ራሳቸውን በቃላት ጋጋታ ሰማይ የሰቀሉ፣ ከኛ በላይ ላሳር የሚሉ ስልጣኔን ከትግራይ ህዝብ እጅ ነስተው የተቀበሉ በእርሻ ሰብል፣ በከብትና በህዝብ ብዛት የሚገነባ የታሪክና የባህል ልቀት ያለ ይመስል አይናቸውን በጨው አጥበው በድርቅና አኮሳሽ ስምና ቅፅል እየለጠፉ አገራዊ ጥላቻን በማነሳሳት የትግራይን ህዝብ ለማጥፋት ከፍተኛ ትግል ይዘዋል። ይህ ትግል አሁን እጅግ መጠነ ሰፊና የአለም መንግስታትን ዲፕሎማሲ ያመሰቃቀለ ሆነ እንጂ ፊትም ቢሆን ከአሁኑ ባነሰ ልኬት ሲደረግ ኖሯል። “ትግሬ አንበጣ ይበላል” ብቻ ሳይሆን ራሱ አንበጣ ነው እያሉ በአንበጣ በሊታ አሞራ ስም የተሰየመ የጦር ዘመቻም ተካሂዶበታል። ባለፈው አመትም ይህ ሰብአዊ ፍጡርነትን የሚገስ ስያሜ ከስንት ዘመን በኋላ እንዳዲስ ተነስቶ ጎንደር ላይ “የመቀሌው፣ አንበጣ በሊታው” እየተባለ ይፎከርና ይቅራራ ነበር። እንደ ጎንደር ሆኖ ያበደ ህዝብ በአለም ላይ ይኖር ይሆን? ለራሱ አላግባብ በሰጠው የበላይነት ስሜት ጎርፍ ተወስዶ የማይመለስበት ገደል ውስጥ ጨምሮታል። ጎንደርን ገንጥሎ ከኤሪትርያ ጋር ለማዋሃድ ድልድይ የሆነችውን ወልቃይትን ከትግራይ ለመዝረፍ ህዝቡን ያስፈጃል። የጎንደር ዳያስፓራ ጂኦፓለቲካዊ ቅዠት! ዘር አጥፊዎቹ ራሳቸውን ሲያታልሉ የትግራይን ህዝብ የገመገሙት በህዝብ ብዛቱ ነው፣ ፔርሻዎች ግሪኮችን በብዛታቸው ብቻ አቅማቸውን እንደ ገመቱት ሁሉ። ፔርሻዎች ያልገባቸው ግሪኮች ለአለም ያበረከቱት የሳይንስ እውቀት ብቻ ሳይሆን የውጊያ ጥበብንም ጭምር እንደ ነበር ነው። ሰውን የሚገድለው አንድ ጠርሙዝ ውሃ ሳይሆን አንዲት ጠብታ መርዝ ናት። በትግራይ በሚደረገው አይነተ ብዙ የዘር ማጥፋት የተከሰተውም ይኸው ነው። የሂሳብ አራት መደብ ጠንቅቆ ያላወቀውም ሳይቀር የትግራይ ህዝብ ስድስት ፐርሰንት ብቻ መሆኑን ያላንፀባረቀ የለም። ዘጠና አራትንና ስድስት ፐርሰንትን እያወዳደረ ሳይዋጋ በህልሙ ድል የተቀዳጀ ቁጥር ስፍር የለውም። አለም አዲስና አንፀባራቂ ታሪክ እየፃፈ ነው። ታሪክ እስከ ቅርቡ የሚያውቃቸው የዘር ማጥፋት ድርጊቶች ከተጠቂዎች በኩል ምንም ግብረ መልስ ባልነበረበት አሳዛኝ ሁኔታ የተፈፀሙ ነበሩ። አርመኖች በቱርኮች ሲጨፈጨፉ ምንም መከታ አልነበራቸውም። ስድስት ሚልዮን አይሁዶች እስኪያልቁ ድረስ የአይሁድ መካች ጦር የሚባል አልነበረም። የአይሁዶች መንግስትም አልተመሰረተም ነበር። ቱትሲዎችም ቢሆኑ ካለቁ በኋላ ነው ታጣቂዎች የደረሱት። የዘር ማጥፋት በተካሄደባቸው ሁሉ ተጠቂው ህዝብ ያለ መከታ እንደ አብርሃም በግ ነበር በዝምታ ሲታረድ የኖረው። ትግራይ ውስጥ እየሆነ ያለው ግን ፍፁም የተለየ ነው። ልዩነቱ ማህበራዊ ዝቅታ ላይ ያለ ህዝብ ማህበራዊ ከፍታ ላይ ያለን ህዝብ በቀላል የስነ ህዝብ ስሌት ላይ ብቻ ተመስርቶ ለማጥፋት መሞከሩ ነው። የዘር ማጥፋት ጦርነቱ በኢትዮጵያ ሃይሎች ብቻ ሳይሆን የውጭ ሃይሎችንም በወሳኝነት ባካተተ መልኩ ተጀምሮ እንደቀጠለ ነው። በትግራይ ላይ ወራሪውን ሃይል ለማበረታታት ሲባል የስነ ህዝብ ስሌት ተሰራና በጥቂት ቀናት ይጠናቀቃል ተባለ እንጂ ይህን ህዝብ አጠፋለሁ ብሎ መነሳት ቀላል እንዳልሆነ ወራሪዎቹ በሚገባ ያውቃሉ። የትግራይን ህዝብ ካላጠፉ ስልጣናቸው ስለማይረጋ ምርጫ የላቸውምና ማንኛውም ዋጋ ለመክፈል ቆርጠው ተነሱ። ዋጋው ሳይውል ሳያድር በጥቂት ወራቶች ውስጥ እየታየ ነው:- የአገሪቱ ኢኮኖሚ ተምዘግዝጎ ወረደ፣ ሰራዊቱ አለቀ፣ የኢትዮጵያ ስም እንዳይመለስ ሆኖ ረከሰ፣ አገሪቱ በነፃነት ሳይሆን በቃለ አባይነት ታወቀች፣ ትምህርትና ማህበራዊ ህይወት ተቃወሰ፣ ጦርነት በመላ አገሪተ ተስፋፋ። ኢትዮጵያ ሆይ! አልነገርኩሽም ወይ ጩኬ በላንቃየ፣ ትግሬን ነክተሽ ሰላም አታገኚም ብየ። ይህ ግጥም ብዙ ነገር ይናገራል። ትግራይን ለመውረር በሰላም ስምና በኖቤል ውስጥ ተሸሽገው የኢትዮጵያን ኢምፔርያሊዝም ማንሰራራት እንዲመሩ የተመረጡት አቢይና ኢሳያስ ሲመክሩና ዝግጅት ሲያጧጥፉ የሚከተለው ጥፋት በግልፅ የታያቸው በርካታ ታላላቅ ሰዎች “ይህ ነገር የማያባራ መአት ያመጣልና ተዉ!” ብለው መክረው ነበር። እብሪቱ ግን “መኖር የሚችሉት ወይ ትግራይ ወይ ኢትዮጵያ እንጂ ሁለቱም አንድ ላይ አይሆንም” የሚል ሆነ። ወይ ጉድ! “ያዳቆነ ሰይጣን ሳያቀስስ አይለቅም” አሉ። የትግራዩ ዘር የማጥፋት ጥረት ልዩ የሚያደርገው የሚፈራውና የሚከበረውን የትግራይን ከፍታ በውሸት ትርክት ዝቅ በማድረግ ህዝብን ማነሳሳቱ ነው። የአገር መከታ መሆንና ኢትዮጵያም በአለም መድረክ ታዋቂና የተከበረች እንድትሆን የማድረጉ፣ እንዲሁም የኢትዮጵያ የክርስትናና የእስልምና ማእከል የመሆኗ ነገር የትግራይ የልእልና ምንጮችና መገለጫዎች ናቸው። ትግራይን ከዚህ ልእልና አውርደው ሳይጥሉ ለዘር ማጥፋት ህዝብን መቀስቀስ ስለማይችሉ የእንስሳና የበሽታ ስም ከመስጠት በላቀ ህዝብን ለበቀል የሚጋብዙ “ትግሬዎች ባንዳ ናቸው! ትግሬዎች ፀረ ሃይማኖት ናቸው” እይሉ ይለፍፋሉ። ትግራይን ከማህበራዊ ከፍታ የማውረድ ዘመቻው በየቀኑ አዳዲስ ክስተቶች የሚያስመዘግብና መገለጫዎቹም በርካታ ናቸው። ተቀድቶ የማያልቁት ውድ የባህል እሴቶችን ለማጥቃት ረዥም ጊዜና ጥረት ይጠይቃል። የሴቶች ነፃነት መገለጫ የሆነው አሸንዳ ከትግራይ ማህበራዊ ከፍታዎች አንዱ ነው። ሰሞኑን እሱንም ደረጃውን ለማሳነስ ተራ የህፃናት ጨዋታ እየተጫወቱ ነው። በኔ ግምት ከእንግዲህ ዘር ማጥፋት በአለም ላይ የትግራዩ የመጨረሻው ሊሆን ይችላል። የአለም ህዝቦች የመጣባቸውን የዘር ማጥፋት መመከት እንዳለባቸው ከትግራዩ ታሪካዊ ልምድ መማር አለባቸው። ትግራይም በዚህ ረገድ ባላት ለጭቁን ህዝብ የመቆርቆር ባህል ለተጠቂዎች ልምድ ለማካፈል ወደኋላ አትልም። ካለፈው ታልቅ ታሪኳ በላቀ ሁኔታ የአለም ጭቁን ህዝቦች የትግል አርአያ ሆና እንደምታንፀባርቅ ፅኑ እምነቴ ነው።
Back to Front Page |